በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አምላክን እና ክርስቶስን በተመለከተ እውነቱ ምንድን ነው?

አምላክን እና ክርስቶስን በተመለከተ እውነቱ ምንድን ነው?

ሰዎች ብዙ አማልክት ያመልካሉ፤ እውነተኛው አምላክ ግን አንድ ብቻ ነው። (ዮሐንስ 17:3) “ከሁሉ የላቀው አምላክ፣” የሁሉም ነገር ፈጣሪ እንዲሁም የሕይወት ሁሉ ምንጭ እሱ ነው። ልናመልክ የሚገባው እሱን ብቻ ነው።—ዳንኤል 7:18፤ ራእይ 4:11

አምላክ ማን ነው?

የአምላክ ስም በበኩረ ጽሑፉ ውስጥ 7,000 ጊዜ ያህል ይገኛል

ይሖዋ የአምላክ ስም ነው

ጌታ፣ አምላክ፣ አብ—የይሖዋ የማዕረግ ስሞች

የአምላክ ስም ማን ነው? አምላክ ራሱ “እኔ ይሖዋ ነኝ። ስሜ ይህ ነው” ብሏል። (ኢሳይያስ 42:8) ይህ የአምላክ ስም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ 7,000 ጊዜ ያህል ተጠቅሷል። ይሁንና ብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞች ይህን ስም “እግዚአብሔር” ወይም “ጌታ” እንደሚሉት ባሉ የማዕረግ ስሞች ያለአግባብ ተክተውታል። አምላክ ወዳጁ እንድትሆን ስለሚፈልግ ‘ስሙን እንድትጠራ’ ግብዣ አቅርቦልሃል።—መዝሙር 105:1

የይሖዋ የማዕረግ ስሞች። መጽሐፍ ቅዱስ ይሖዋን “አምላክ፣” “ሁሉን ቻይ፣” “ፈጣሪ፣” “አብ፣” “ጌታ” እና “ልዑል” እንደሚሉት ባሉ የማዕረግ ስሞች ይጠራዋል። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ተመዝግበው በሚገኙ በርካታ ጸሎቶች ላይ እንደምናነበው ሰዎች የይሖዋን የግል ስም ከማዕረግ ስሞቹ ጋር አጣምረው ተጠቅመውበታል።—ዳንኤል 9:4

የአምላክ ገጽታ። አምላክ በዓይን የማይታይ መንፈስ ነው። (ዮሐንስ 4:24) መጽሐፍ ቅዱስ “አምላክን ያየው አንድም ሰው የለም” ይላል። (ዮሐንስ 1:18) ሆኖም መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ ስሜት እንዳለው ይናገራል። ሰዎች ሊያሳዝኑት ወይም ‘ደስ ሊያሰኙት’ ይችላሉ።—ምሳሌ 11:20፤ መዝሙር 78:40, 41

የአምላክ አስደናቂ ባሕርያት። አምላክ አያዳላም፤ የተለያየ ዘር፣ አስተዳደግና ባሕል ያላቸውን ሰዎች በእኩል ዓይን ይመለከታል። (የሐዋርያት ሥራ 10:34, 35) እንዲሁም “መሐሪና ሩኅሩኅ . . . ለቁጣ የዘገየ፣ ታማኝ ፍቅሩና እውነቱ እጅግ ብዙ የሆነ” አምላክ ነው። (ዘፀአት 34:6, 7) ሆኖም ከአምላክ ባሕርያት መካከል አራቱ ይበልጥ ትኩረት የሚስቡ ናቸው።

ኃይል። ይሖዋ “ሁሉን ቻይ አምላክ” ስለሆነ የገባውን ቃል በሙሉ ለመፈጸም የሚያስችል ገደብ የለሽ ኃይል አለው።—ዘፍጥረት 17:1

ጥበብ። አምላክ በጥበቡ ተወዳዳሪ የለውም። መጽሐፍ ቅዱስ “እሱ ብቻ ጥበበኛ” እንደሆነ የሚናገረው ለዚህ ነው።—ሮም 16:27

ፍትሕ። አምላክ ምንጊዜም የሚያደርገው ትክክል የሆነውን ነገር ነው። ሥራው ሁሉ “ፍጹም” ነው፤ እንዲሁም “ፈጽሞ ፍትሕን የማያጓድል” አምላክ ነው።—ዘዳግም 32:4

ፍቅር። መጽሐፍ ቅዱስ “አምላክ ፍቅር ነው” በማለት ይናገራል። (1 ዮሐንስ 4:8) አምላክ ፍቅር ከማሳየትም ባለፈ እሱ ራሱ ፍቅር ነው። አምላክ ሁሉንም ነገር የሚያደርገው ወደር የለሽ በሆነው ፍቅሩ ተነሳስቶ ነው፤ ይህም ለእኛ ብዙ ጥቅም አስገኝቶልናል።

አምላክ ከሰዎች ጋር ያለው ወዳጅነት። አምላክ በሰማይ የሚኖር አፍቃሪ አባታችን ነው። (ማቴዎስ 6:9) በእሱ የምንታመን ከሆነ ወዳጆቹ መሆን እንችላለን። (መዝሙር 25:14) አምላክ በጸሎት አማካኝነት ወደ እሱ እንድንቀርብ ጋብዞናል፤ እንዲሁም መጽሐፍ ቅዱስ “የሚያስጨንቃችሁንም ነገር ሁሉ በእሱ ላይ ጣሉ፤ ምክንያቱም እሱ ስለ እናንተ ያስባል” ይላል።—1 ጴጥሮስ 5:7፤ ያዕቆብ 4:8

በይሖዋ እና በክርስቶስ መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው?

ኢየሱስ ይሖዋ አይደለም። ኢየሱስ ከሌሎች ፍጥረታት ሁሉ የተለየ ነው፤ ምክንያቱም ይሖዋ በቀጥታ የፈጠረው እሱን ብቻ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስ የአምላክ ልጅ እንደሆነ የሚናገረው ለዚህ ነው። (ዮሐንስ 1:14) ይሖዋ የበኩር ልጁ የሆነውን ኢየሱስን ከፈጠረ በኋላ ሌሎች ፍጥረታትን ሁሉ የፈጠረው “የተዋጣለት ሠራተኛ” በሆነው በኢየሱስ አማካኝነት ነው።—ምሳሌ 8:30, 31፤ ቆላስይስ 1:15, 16

ኢየሱስ ከይሖዋ ጋር እኩል እንደሆነ ተናግሮ አያውቅም። ከዚህ ይልቅ “[የአምላክ] ተወካይ ሆኜ የመጣሁ ስለሆንኩ አውቀዋለሁ፤ የላከኝም እሱ ነው” በማለት ተናግሯል። (ዮሐንስ 7:29) እንዲያውም በአንድ ወቅት “ወደ አባቴና ወደ አባታችሁ፣ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ” የሚል አገላለጽ ተጠቅሞ ነበር። (ዮሐንስ 20:17) ኢየሱስ ከሞተ በኋላ ይሖዋ ያስነሳው ሲሆን በሰማይ ላይ በቀኙ አስቀምጦታል እንዲሁም ትልቅ ሥልጣን ሰጥቶታል።—ማቴዎስ 28:18፤ የሐዋርያት ሥራ 2:32, 33

ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ አምላክ እንድትቀርብ ይረዳሃል

ኢየሱስ ወደ ምድር የመጣው ስለ አባቱ ሊያስተምረን ነው። ይሖዋ ራሱ ስለ ኢየሱስ ሲናገር “የምወደው ልጄ ይህ ነው። እሱን ስሙት” ብሏል። (ማርቆስ 9:7) የኢየሱስን ያህል ይሖዋን የሚያውቀው ማንም የለም። ኢየሱስ “ከወልድና ወልድ ሊገልጥለት ከሚፈቅድ በስተቀር አብ ማን እንደሆነ የሚያውቅ የለም” በማለት ተናግሯል።—ሉቃስ 10:22

ኢየሱስ የይሖዋን ባሕርያት ፍጹም በሆነ መንገድ አንጸባርቋል። ኢየሱስ የአባቱን ባሕርያት ፍጹም በሆነ መንገድ በማንጸባረቁ “እኔን ያየ ሁሉ አብንም አይቷል” ሊል ችሏል። (ዮሐንስ 14:9) ኢየሱስ በንግግሩም ሆነ በድርጊቱ የአባቱን ፍቅር በማንጸባረቅ ሰዎች ወደ ይሖዋ እንዲቀርቡ ረድቷቸዋል። እንዲህ ብሏል፦ “እኔ መንገድ፣ እውነትና ሕይወት ነኝ። በእኔ በኩል ካልሆነ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም።” (ዮሐንስ 14:6) በተጨማሪም እንዲህ በማለት ተናግሯል፦ “እውነተኛ አምላኪዎች አብን በመንፈስና በእውነት የሚያመልኩበት ሰዓት ይመጣል፤ . . . አብ እንዲያመልኩት የሚፈልገው እንዲህ ያሉ ሰዎችን ነው።” (ዮሐንስ 4:23) እስቲ አስበው! ይሖዋ ስለ እሱ እውነቱን ማወቅ የሚፈልጉ እንደ አንተ ያሉ ሰዎች እንዲያመልኩት ይፈልጋል።