በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከዓለም አካባቢ

የዜናው ትኩረት—አፍሪካ

የዜናው ትኩረት—አፍሪካ

ብዙ ድርጅቶችና ግለሰቦች ዛሬም የአፍሪካውያንን ኑሮ ለማሻሻል ጥረት ማድረጋቸውን አላቆሙም። ይሁን እንጂ ይህ አህጉር ዛሬም መውጫ የሌላቸው በሚመስሉ ችግሮች ውስጥ እንደተዘፈቀ ነው።

የአውራሪስ ሕገ ወጥ አደን

በ2013 በደቡብ አፍሪካ፣ በአጠቃላይ 1,004 አውራሪሶች በሕገ ወጥ አዳኞች ተገድለዋል፤ በ2007 በዚህ መንገድ የተገደሉት ግን 13 ብቻ ነበሩ። የአውራሪስ ቀንድ አቅርቦት በዚህ መጠን ቢጨምርም ተፈላጊነቱም በዚያው ልክ እያደገ በመሄዱ የአውራሪስ ቀንድ ዋጋ (በኪሎ ግራም) ከወርቅ የበለጠ የሚያወጣ ሆኗል። አንድ የአውራሪስ ቀንድ እስከ ግማሽ ሚሊዮን ዶላር ሊሸጥ ይችላል።

እስቲ አስበው፦ መንግሥታት ሕገ ወጥነትን ሙሉ በሙሉ ማስወገድ ይችላሉ? —ኤርምያስ 10:23

ጉቦኞችን አለማጋለጥ

ራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል የተባለው ድርጅት እንደገለጸው በዓለም ላይ ጉቦ በስፋት ከሚፈጸምባቸው አገሮች መካከል የምሥራቅ አፍሪካ አገሮች ይገኙበታል። ሆኖም በእነዚህ አገሮች ውስጥ ጉቦ እንዲሰጡ ከሚጠየቁት ሰዎች መካከል 90 በመቶ ገደማ የሚሆኑት ያጋጠማቸውን ሁኔታ ሪፖርት አያደርጉም። በኬንያ የሚገኘው የዚህ ድርጅት ቅርንጫፍ ቢሮ ቃል አቀባይ እንዲህ በማለት ተናግረዋል፦ “ዜጎች የተፈጸመውን ሙስና ሪፖርት ቢያደርጉም የአገራቸው መንግሥት በሙሰኞቹ ላይ እርምጃ ይወስዳል ብለው አያምኑም።”

መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “ጕቦ፣ አጥርተው የሚያዩትን ሰዎች ዐይን ያሳውራል።”—ዘፀአት 23:8

የኢንተርኔት ተጠቃሚ የሆኑ አፍሪካውያን

ዓለም አቀፍ የቴሌኮሙኒኬሽን ማኅበር እንደገለጸው እስከ 2014 መጨረሻ ድረስ 20 በመቶ የሚሆኑ አፍሪካውያን የኢንተርኔት ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ይጠበቃል። በሞባይል የኢንተርኔት አገልግሎት ለማግኘት የሚጠይቁ ደንበኞች ብዛት በጣም እየጨመረ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ከዓለም አቀፉ አማካይ ጭማሪ በእጥፍ ይበልጣል።