በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የሰው ልጆችን ይወዳል

የሰው ልጆችን ይወዳል

“በተለይ . . . በሰው ልጆች እጅግ እደሰት ነበር።”—ምሳሌ 8:31

1, 2. ኢየሱስ ለሰው ልጆች ጥልቅ ፍቅር እንዳለው የሚያሳየው አንዱ ማስረጃ ምንድን ነው?

ጥልቅ የሆነው የይሖዋ ጥበብ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ እንዲሁም ሙሉ በሙሉ የተገለጠው በአምላክ የበኩር ልጅ ላይ ነው። ኢየሱስ በጥበብ የተመሰለ ሲሆን “የተዋጣለት ሠራተኛ” ሆኖ ከአባቱ ጎን ነበር። አባቱ “ሰማያትን ባዘጋጀ” ብሎም “የምድርን መሠረቶች ባቆመ ጊዜ” ኢየሱስ ምን ያህል ተደስቶና ሐሴት አድርጎ እንደሚሆን እስቲ አስበው። ይሁንና የአምላክ የበኩር ልጅ ግዑዛን ነገሮችን ቢያደንቅም ‘በተለይ በሰው ልጆች እጅግ ይደሰት ነበር።’ (ምሳሌ 8:22-31) በእርግጥም ኢየሱስ ሰው ከመሆኑ በፊትም ለሰው ልጆች ጥልቅ ፍቅር ነበረው።

2 የአምላክ የበኩር ልጅ ከጊዜ በኋላም ለአባቱ ያለውን ፍቅርና ታማኝነት እንዲሁም ‘ለሰው ልጆች’ ያለውን ጥልቅ ፍቅር ለማሳየት ሲል በፈቃደኝነት “ራሱን ባዶ በማድረግ” ሰው ሆኖ ወደ ምድር መጥቷል። ይህን ያደረገው “በብዙ ሰዎች ምትክ ሕይወቱን ቤዛ አድርጎ ለመስጠት” ነው። (ፊልጵ. 2:5-8፤ ማቴ. 20:28) በእርግጥም ለሰው ልጆች ታላቅ ፍቅር አለው! ኢየሱስ ምድር ላይ በነበረበት ወቅት አምላክ ተአምር የመፈጸም ኃይል ሰጥቶታል፤ እነዚህ ተአምራት ደግሞ ኢየሱስ ሰዎችን ምን ያህል እንደሚወድ አሳይተዋል። ኢየሱስ ያከናወነው ነገር በቅርቡ በመላዋ ምድር ምን ዓይነት አስደናቂ ተአምራት እንደሚፈጸሙ ሠርቶ ማሳያ ነው።

3. በዚህ ርዕስ ውስጥ ትኩረት የምናደርገው በምን ላይ ነው?

3 ኢየሱስ ወደ ምድር መምጣቱ “የአምላክን መንግሥት ምሥራች ማወጅ” እንዲችልም አጋጣሚ ከፍቶለታል። (ሉቃስ 4:43) ኢየሱስ፣ ይህ መንግሥት የአባቱን ስም እንደሚያስቀድስና የሰው ልጆች ለሚያጋጥሟቸው ችግሮች ሁሉ ዘላቂ መፍትሔ እንደሚያስገኝ ያውቅ ነበር። ከቦታ ቦታ እየተጓዘ መስበኩን የሚገልጹትን ዘገባዎች ስንመረምር ለሰው ዘር ቤተሰብ ከልብ እንደሚያስብ የሚያረጋግጡ በርካታ ማስረጃዎች እናገኛለን። ለመሆኑ ይህ ጉዳይ ትኩረታችንን የሚስበው ለምንድን ነው? ምክንያቱም ከእነዚህ ዘገባዎች የምናገኘው ትምህርት የወደፊቱን ጊዜ በልበ ሙሉነት እና በተስፋ ለመጠባበቅ ያስችለናል። እስቲ ኢየሱስ ከፈጸማቸው ተአምራት አራቱን እንመርምር።

‘ለመፈወስ የሚያስችለው ኃይል ከኢየሱስ ጋር ነበር’

4. ኢየሱስ የሥጋ ደዌ ካለበት ሰው ጋር በተገናኘበት ጊዜ የነበረውን ሁኔታ ግለጽ።

4 ኢየሱስ አገልግሎቱን ከጀመረ ትንሽ ቆየት ብሏል፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ትኩረት ያደረገው በገሊላ ላይ ነው። ኢየሱስ በዚያ ከሚገኙት ከተሞች በአንዱ ውስጥ የሚያሳዝን ነገር ተመለከተ። (ማር. 1:39, 40) በሥጋ ደዌ በሽታ የተያዘ አንድ ሰው አየ፤ ይህ የሚያስፈራ በሽታ ነው። ሐኪሙ ሉቃስ ስለ ሰውየው ሲናገር “መላ ሰውነቱን የሥጋ ደዌ የወረሰው ሰው” ማለቱ ሕመሙ የከፋ ደረጃ ላይ መድረሱን ይጠቁማል። (ሉቃስ 5:12) በሥጋ ደዌ የተያዘው ሰው “ኢየሱስን ባየው ጊዜ በግንባሩ ተደፍቶ ‘ጌታ ሆይ፣ ብትፈልግ እኮ ልታነጻኝ ትችላለህ’ ሲል ለመነው።” ሰውየው፣ ኢየሱስ እሱን የመፈወስ ኃይል እንዳለው አልተጠራጠረም፤ ሆኖም እሱን ለመፈወስ ፍላጎት ያለው መሆኑን ማወቅ ፈልጓል። ታዲያ ኢየሱስ ለዚህ አሳዛኝ ልመና ምን ምላሽ ሰጠ? በበሽታው ምክንያት መልኩ ተበላሽቶ ሊሆን የሚችለውን ይህን ሰው ሲመለከት ምን አስቦ ይሆን? ኢየሱስ፣ በዚህ በሽታ በተያዙ ሰዎች ላይ እንደሚጨክኑት እንደ ፈሪሳውያን ዓይነት አመለካከት ይኖረው ይሆን? አንተ ብትሆን ኖሮ ምን ታደርግ ነበር?

5. ኢየሱስ በሥጋ ደዌ የተያዘውን ሰው ሲፈውስ “እፈልጋለሁ!” እንዲል ያነሳሳው ምንድን ነው?

5 በሥጋ ደዌ የተያዘው ይህ ሰው የሙሴ ሕግ በሚያዘው መሠረት “ርኩስ ነኝ፣ ርኩስ ነኝ!” ብሎ መጮኽ ነበረበት፤ እሱ ግን እንዲህ ያደረገ አይመስልም። ኢየሱስም ይህን ጉዳይ ከማንሳት ይልቅ ትኩረት ያደረገው በሰውየውና በሚያስፈልገው ነገር ላይ ነው። (ዘሌ. 13:43-46) በወቅቱ ኢየሱስ ምን እንዳሰበ በእርግጠኝነት ማወቅ ባንችልም ምን እንደተሰማው ግን እናውቃለን። ኢየሱስ በርኅራኄ ተነሳስቶ ለማሰብ የሚከብድ ነገር አደረገ። እጁን ዘርግቶ ሕመምተኛውን ሰው ከዳሰሰው በኋላ “እፈልጋለሁ! ንጻ” አለው፤ የድምፁ ቃና እርግጠኝነትና አሳቢነት የሚንጸባረቅበት እንደሚሆን ጥርጥር የለውም። ሰውየው “ወዲያውኑ የሥጋ ደዌው ለቀቀው።” (ሉቃስ 5:13) በእርግጥም ኢየሱስ እንዲህ ያለ ተአምር ለመፈጸም ብቻ ሳይሆን ሰዎችን ምን ያህል እንደሚወድ ለማሳየትም ጭምር የሚያስችለው የይሖዋ ኃይል ከእሱ ጋር ነበር።—ሉቃስ 5:17

6. ኢየሱስ የፈጸማቸው ተአምራት አስገራሚ የሆኑት ለምንድን ነው? ምንስ ያስተምሩናል?

6 ኢየሱስ ክርስቶስ በአምላክ ኃይል ተጠቅሞ እጅግ የሚያስገርሙ የተለያዩ ተአምራትን ፈጽሟል። በሥጋ ደዌ የተያዙ ሰዎችን ብቻ ሳይሆን በሕዝቡ መካከል ያለውን ማንኛውንም ዓይነት በሽታና ማንኛውንም ዓይነት ሕመም ፈውሷል። በመንፈስ መሪነት የተጻፈው ዘገባ “ሕዝቡም ዱዳዎች ሲናገሩ፣ ሽባዎች ሲፈወሱ፣ አንካሶች ሲራመዱና ዓይነ ስውሮች ሲያዩ ተመልክተው እጅግ ተደነቁ” ይላል። (ማቴ. 15:31) ኢየሱስ እንዲህ ዓይነት የርኅራኄ ተግባር ለመፈጸም፣ የሰውነት ክፍል የሚለግሱ ሰዎች አላስፈለጉትም። ምክንያቱም የፈወሰው፣ ጉዳት የደረሰባቸውን የአካል ክፍሎች ነው። ከዚህም ሌላ ሰዎችን ወዲያውኑ የፈወሰ ሲሆን አጠገቡ የሌሉ ሕመምተኞችን እንኳ ያዳነበት ጊዜ አለ። (ዮሐ. 4:46-54) እነዚህ አስደናቂ ዘገባዎች ምን ያስተምሩናል? አሁን በሰማይ ንጉሥ የሆነው ኢየሱስ ዘላቂ ፈውስ ለማምጣት ኃይል ብቻ ሳይሆን ፍላጎትም ጭምር እንዳለው ይጠቁሙናል። ኢየሱስ ሰዎችን የያዘበትን መንገድ ማወቃችን “ለችግረኛውና ለድሃው ያዝናል” የሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት በአዲሱ ዓለም ውስጥ እንደሚፈጸም እንድንተማመን ያደርገናል። (መዝ. 72:13) በእርግጥም በዚያን ጊዜ ኢየሱስ የተቸገሩትን ሁሉ የመርዳት ልባዊ ፍላጎቱን ያሳካል።

“ተነስ! ምንጣፍህን ተሸክመህ ሂድ”

7, 8. ኢየሱስ በቤተዛታ የውኃ ገንዳ አጠገብ ከአንድ የታመመ ሰው ጋር የተገናኘው እንዴት እንደሆነ ግለጽ።

7 ኢየሱስ በሥጋ ደዌ የተጠቃውን ሰው በገሊላ ከፈወሰ ጥቂት ወራት አልፈዋል። የአምላክን መንግሥት ምሥራች ለመስበክና ለማወጅ ከገሊላ ወደ ይሁዳ ሄደ። የኢየሱስ መልእክትና ያከናወናቸው ነገሮች በሺዎች በሚቆጠሩ ሰዎች ሕይወት ላይ በጎ ተጽዕኖ አሳድረው መሆን አለበት። ለድሆች ምሥራቹን መናገር፣ ለተማረኩት ነፃነትን ማወጅና ልባቸው የተሰበረውን መጠገን እንደሚፈልግ በግልጽ አሳይቷል።—ኢሳ. 61:1, 2፤ ሉቃስ 4:18-21

8 አሁን ወሩ ኒሳን ነው። ኢየሱስ የአባቱን ትእዛዝ በማክበር ለፋሲካ በዓል ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ። ሕዝቡ ይህን ቅዱስ በዓል ለማክበር ወደ ኢየሩሳሌም ስለመጡ ከተማዋ ሞቅ ብላለች። ከቤተ መቅደሱ በስተ ሰሜን ቤተዛታ የሚባል የውኃ ገንዳ ይገኛል፤ በዚያም ኢየሱስ አንድ የታመመ ሰው አገኘ።

9, 10. (ሀ) ሰዎች ወደ ቤተዛታ የውኃ ገንዳ የሚመጡት ለምን ነበር? (ለ) ኢየሱስ በገንዳው አጠገብ ምን አደረገ? ይህ ዘገባ ምን ያስተምረናል? (በመግቢያው ላይ ያለውን ሥዕል ተመልከት።)

9 የታመሙ በርካታ ሰዎች በቤተዛታ አካባቢ ይሰበሰቡ ነበር። ወደዚያ ቦታ የሚመጡት ለምንድን ነው? ሕዝቡ፣ አንድ የታመመ ሰው ውኃው በሚናወጥበት ጊዜ ገንዳው ውስጥ ቢገባ በተአምር እንደሚፈወስ ስለሚያምኑ ነው፤ እርግጥ ለዚህ እምነት መሠረት የሆነው ምን እንደሆነ ዘገባው አይገልጽም። በአካባቢው ምን ዓይነት ድባብ ሰፍኖ እንደሚሆን ለማሰብ ሞክር። ብዙዎች የተስፋ መቁረጥና የጭንቀት ስሜት ይታይባቸዋል። ታዲያ ምንም ዓይነት የጤና እክል የሌለበት ፍጹም ሰው የሆነው ኢየሱስ ወደዚያ የሄደው ለምንድን ነው? ኢየሱስ፣ እሱ በምድር ላይ ከኖረበት ለሚበልጡ ዓመታት ታሞ ወደ ቆየ አንድ ሰው የቀረበው በርኅራኄ ስሜት ተገፋፍቶ ነው።ዮሐንስ 5:5-9ን አንብብ።

10 ኢየሱስ፣ ሰውየውን መዳን ይፈልግ እንደሆነ ሲጠይቀው በታመመው ሰው ፊት ላይ የሚነበበውን የተስፋ መቁረጥ ስሜት በዓይነ ሕሊናህ መሳል ትችላለህ? ሰውየው ወዲያውኑ ምላሽ ሰጠው። ሕመምተኛው መዳን ቢፈልግም እንኳ ገንዳው ውስጥ ለመግባት የሚረዳው ሰው ስለሌለ ምን ማድረግ እንዳለበት ግራ እንደገባው ገለጸ። በዚህ ጊዜ ኢየሱስ፣ ሰውየውን ለማመን የሚከብድ ነገር እንዲያደርግ ይኸውም ምንጣፉን ተሸክሞ እንዲሄድ አዘዘው። ሰውየውም ኢየሱስ ያለውን በማመን ምንጣፉን አንስቶ መሄድ ጀመረ። ይህ ኢየሱስ በአዲሱ ዓለም ውስጥ ለሚያደርገው ነገር ናሙና የሚሆን እንዴት ያለ አስደሳች ድርጊት ነው! ይህ ተአምር ኢየሱስ ሩኅሩኅ መሆኑንም ያሳያል። እርዳታ የሚያስፈልጋቸውን ሰዎች ፈልጎ ያገኝ ነበር። የኢየሱስ ምሳሌ እኛም በክልላችን ውስጥ ያሉ በዚህ ዓለም በሚፈጸሙት መጥፎ ነገሮች ያዘኑ ሰዎችን መፈለጋችንን እንድንቀጥል ሊያነሳሳን ይገባል።

“ልብሴን የነካው ማን ነው?”

11. ማርቆስ 5:25-34 ኢየሱስ ለታመሙ ሰዎች ያለውን ርኅራኄ የሚያጎላው እንዴት ነው?

11 ማርቆስ 5:25-34ን አንብብ። ይህች ሴት ለ12 ዓመታት የኖረችው ተሸማቃ ነው። ያለባት የጤና እክል አምልኮዋን ጨምሮ በመላው ሕይወቷ ላይ ተጽዕኖ አሳድሯል። “ይህች ሴት በርካታ ሐኪሞች ጋር የሄደች ሲሆን ሕክምናው ለብዙ ሥቃይ ዳርጓት ነበር፤ ያላትን ጥሪት ሁሉ ብትጨርስም ሕመሙ ባሰባት።” ሆኖም አንድ ቀን ከሕመሟ መፈወስ የምትችልበት ሌላ መንገድ እንዳለ አሰበች። ኢየሱስ የሚባለው ሰው አጠገብ ለመሆን ወሰነች። በመሆኑም በሕዝቡ መሃል አልፋ በመሄድ የኢየሱስን ልብስ ነካች። (ዘሌ. 15:19, 25) ኢየሱስ ኃይል ከእሱ እንደወጣ ታወቀው፤ በመሆኑም “ልብሴን የነካው ማን ነው?” ብሎ ጠየቀ። ሴትየዋም “በፍርሃት እየተንቀጠቀጠች መጥታ በፊቱ ተደፋች፤ ከዚያም ምንም ሳታስቀር እውነቱን ነገረችው።” ኢየሱስ፣ ሴትየዋን የፈወሳት አባቱ ይሖዋ እንደሆነ ስለተገነዘበ በደግነት “ልጄ ሆይ፣ እምነትሽ አድኖሻል። በሰላም ሂጂ፤ ከሚያሠቃይ ሕመምሽም ተፈወሽ” አላት።

ኢየሱስ ስለ እኛም ሆነ ስላሉብን ችግሮች እንደሚያስብ በፈጸማቸው ተአምራት አማካኝነት አሳይቷል (አንቀጽ 11, 12ን ተመልከት)

12. (ሀ) እስካሁን ከተመለከትናቸው ነጥቦች አንጻር ኢየሱስን እንዴት ትገልጸዋለህ? (ለ) ኢየሱስ ምን ምሳሌ ትቶልናል?

12 ኢየሱስ እንዴት ደግ ነው! በሕመም ለሚሠቃዩ ሰዎች የሚራራ አንጀት እንዳለው መመልከት እንችላለን። ሰይጣን የማንፈለግና ዋጋ የሌለን ሆኖ እንዲሰማን ለማድረግ ይጥራል። ይሁንና ኢየሱስ ስለ እኛም ሆነ ስላሉብን ችግሮች እንደሚያስብ በፈጸማቸው ተአምራት አማካኝነት በግልጽ አሳይቷል። ንጉሣችንና ሊቀ ካህናችን ምንኛ ሩኅሩኅ ነው! (ዕብ. 4:15) ከባድ የጤና እክል ያለባቸውን ሰዎች ስሜት መረዳት፣ በተለይ ደግሞ እኛ እንዲህ ያለ ሁኔታ አጋጥሞን የማያውቅ ከሆነ ይቸግረን ይሆናል። ኢየሱስ ግን እሱ ራሱ ታሞ ባያውቅም እንኳ የታመሙ ሰዎችን ስሜት ይረዳ እንደነበር ማስታወስ ይኖርብናል። የኢየሱስ ምሳሌ እኛም አቅማችን በሚፈቅደው መጠን እንዲሁ እንድናደርግ ሊያነሳሳን ይገባል።—1 ጴጥ. 3:8

“ኢየሱስም እንባውን አፈሰሰ”

13. ኢየሱስ አልዓዛርን ከሞት ማስነሳቱ ምን ዓይነት ባሕርይ እንዳለው ያሳያል?

13 ኢየሱስ የሌሎችን ሥቃይ ሲመለከት ከልቡ ያዝን ነበር። ወዳጁ አልዓዛር በመሞቱ ሌሎች ምን ያህል እንዳዘኑ ሲያይ ስሜቱ በጥልቅ በመነካቱ “እጅግ አዘነ፤ ተረበሸም።” እንዲህ የተሰማው፣ አልዓዛርን ከጥቂት ጊዜ በኋላ ከሞት እንደሚያስነሳው እያወቀ ነው። (ዮሐንስ 11:33-36ን አንብብ።) ኢየሱስ፣ በጣም እንዳዘነ ሰዎች ማየታቸው አላሳፈረውም። በዙሪያው የነበሩት ሰዎች ኢየሱስ ለአልዓዛርና ለቤተሰቡ ያለውን ፍቅር ማየት ይችሉ ነበር። ኢየሱስ ከአምላክ ያገኘውን ኃይል ተጠቅሞ ወዳጁን ከሞት በማስነሳት ሩኅሩኅ መሆኑን አሳይቷል።—ዮሐንስ 11:43, 44

14, 15. (ሀ) ይሖዋ፣ የሰው ልጆች ያለባቸውን መከራ ለማስወገድ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳለው የሚያሳየው ምንድን ነው? (ለ) “በመታሰቢያ መቃብር” የሚለው አገላለጽ ትኩረታችንን የሚስበው ለምንድን ነው?

14 መጽሐፍ ቅዱስ፣ ስለ ኢየሱስ ሲናገር የፈጣሪ ‘ማንነት ትክክለኛ አምሳያ’ መሆኑን ይገልጻል። (ዕብ. 1:3) በመሆኑም ኢየሱስ የፈጸማቸው ተአምራት እሱም ሆነ አባቱ፣ በሽታና ሞት የሚያስከትሉትን ሥቃይ የማስወገድ ፍላጎት እንዳላቸው ያረጋግጣሉ። ይሖዋና ኢየሱስ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ተመዝግበው የምናገኛቸውን ጥቂት ትንሣኤዎች በማከናወን ብቻ አይገደቡም። ኢየሱስ “በመታሰቢያ መቃብር ያሉ ሁሉ . . . ይወጣሉ” ብሏል።—ዮሐ. 5:28, 29

15 ኢየሱስ “በመታሰቢያ መቃብር” የሚለውን አገላለጽ መጠቀሙ ተገቢ ነው፤ ምክንያቱም ከሞት የሚነሱት በአምላክ መታሰቢያ ያሉ ሰዎች ናቸው። ግዙፍ የሆነውን አጽናፈ ዓለም የፈጠረው ሁሉን ቻይ አምላክ፣ በሞት ካጣናቸው የምንወዳቸው ሰዎች ጋር በተያያዘ እያንዳንዱን ዝርዝር ጉዳይ ያስታውሳል፤ ይህም በተፈጥሮ ያገኟቸውንም ሆነ ከጊዜ በኋላ ያዳበሯቸውን ባሕርያት ያካትታል። (ኢሳ. 40:26) ይሖዋ እነዚህን ሰዎች ማስታወስ ይችላል፤ ከዚህም በላይ እሱም ሆነ ልጁ ይህን ማድረግ ይፈልጋሉ። የአልዓዛርም ሆነ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተመዘገቡት የሌሎች ሰዎች ትንሣኤ፣ በአዲሱ ዓለም ውስጥ በመላው ምድር ለሚከናወነው ነገር ናሙና ነው።

የኢየሱስ ተአምራት ለአንተ ምን ትርጉም አላቸው?

16. በዘመናችን ያሉ ንጹሕ አቋማቸውን የሚጠብቁ በርካታ ክርስቲያኖች ምን መብት ያገኛሉ?

16 ንጹሕ አቋማችንን ጠብቀን የምንመላለስ ከሆነ እስከ ዛሬ ከተፈጸሙት ታላላቅ ተአምራት አንዱ የሆነውን ተአምር በዓይናችን ማየት ይኸውም ታላቁን መከራ በሕይወት ማለፍ እንችላለን። የአርማጌዶን ጦርነት ከተካሄደ ብዙም ሳይቆይ፣ የሰው ልጆች የተሟላ ጤንነት እንዲኖራቸው የሚያደርጉ ተጨማሪ ተአምራት ይከናወናሉ። (ኢሳ. 33:24፤ 35:5, 6፤ ራእይ 21:4) ሰዎች መነጽራቸውን፣ ከዘራቸውን፣ ምርኩዛቸውን፣ ተሽከርካሪ ወንበራቸውን፣ ለመስማት የሚረዷቸውን መሣሪያዎችና እነዚህን የመሳሰሉትን ነገሮች ሲጥሉ በዓይነ ሕሊናህ ይታይህ። ደግሞም ይሖዋ ከአርማጌዶን የሚተርፉት ሰዎች ጥሩ ጤንነት እንዲኖራቸው ማድረጉ የተገባ ነው። ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች የሚጠብቃቸው ሥራ አለ። የአምላክ ስጦታ የሆነችውን ምድራችንን ወደ ገነትነት የመቀየሩን ሥራ በቅንዓት ማከናወን ይችላሉ።—መዝ. 115:16

17, 18. (ሀ) ኢየሱስ ተአምራት የፈጸመው ለምንድን ነው? (ለ) ወደ አምላክ አዲስ ዓለም ለመግባት ጥረት ማድረግ ያለብህ ለምንድን ነው?

17 ኢየሱስ ምድር ላይ በነበረበት ጊዜ ሕመምተኞችን መፈወሱ፣ በዘመናችን ያሉ ‘የእጅግ ብዙ ሕዝብ’ አባላት ከማንኛውም በሽታ እንደሚፈወሱ ባላቸው አስደሳች ተስፋ ላይ ይበልጥ እንዲተማመኑ ያደርጋቸዋል። (ራእይ 7:9) የአምላክ የበኩር ልጅ የታመሙትን መፈወሱ ለሰው ልጆች በጥልቅ እንደሚያስብና በጣም እንደሚወዳቸው ያሳያል። (ዮሐ. 10:11፤ 15:12, 13) ኢየሱስ ያሳየው ርኅራኄ ይሖዋ ለእያንዳንዱ አገልጋዩ እንደሚያስብ የሚያረጋግጥ ልብ የሚነካ ማስረጃ ነው።—ዮሐ. 5:19

18 የሰው ዘር እየቃተተና እየተሠቃየ እንዲሁም በሞት እየተቀጠፈ ነው። (ሮም 8:22) አምላክ ቃል በገባው መሠረት የተሟላ ፈውስ የምናገኝበት የአምላክ አዲስ ዓለም ያስፈልገናል። ሚልክያስ 4:2 ፈውስ ያገኙ ሰዎች ‘እንደሰቡ ጥጆች እንደሚቦርቁ’ ይኸውም ፍጹም አለመሆናቸው ካመጣባቸው ባርነት ነፃ በመውጣታቸው እንደሚደሰቱ ተስፋ ይሰጠናል። ለአምላክ ያለን ልባዊ አመስጋኝነትና እሱ በሰጣቸው ተስፋዎች ላይ ያለን ጠንካራ እምነት በአዲሱ ዓለም ውስጥ ለመኖር የሚያስፈልጉትን ብቃቶች ለማሟላት የምንችለውን ሁሉ እንድናደርግ የሚያነሳሳን ይሁን። ኢየሱስ ምድር ላይ በነበረበት ጊዜ የፈጸማቸው ተአምራት በመሲሐዊ አገዛዙ ሥር የሰው ዘር በቅርቡ ለሚያገኘው ዘላቂ እፎይታ ቅምሻ እንደሆኑ ማወቁ ምንኛ የሚያስደስት ነው!