ፀረ ክርስቶስ ማን ነው?
መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?
ፀረ ክርስቶስ ሲባል እንዲሁ አንድን ግለሰብ ወይም አንድን ቡድን ብቻ የሚያመለክት አይደለም፤ ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ “ብዙ ፀረ ክርስቶሶች” እንዳሉ ይናገራል። (1 ዮሐንስ 2:18) “የክርስቶስ ተቃዋሚ” የሚል ትርጉም ያለው “ፀረ ክርስቶስ” የተባለው አገላለጽ የሚከተሉትን ነገሮች የሚያደርግን ማንኛውም ሰው የሚያመለክት ነው፦
ኢየሱስ፣ ክርስቶስ ወይም መሲሕ መሆኑን ይክዳል፤ እንዲሁም የአምላክ ልጅ መሆኑን ይክዳል።—1 ዮሐንስ 2:22
አምላክ የቀባውን ክርስቶስን ይቃወማል።—መዝሙር 2:1, 2፤ ሉቃስ 11:23
ክርስቶስ ነኝ ይላል።—ማቴዎስ 24:24
የክርስቶስን ተከታዮች ያሳድዳል፤ ምክንያቱም ኢየሱስ በእነሱ ላይ የሚደረገውን ነገር በእሱ ላይ እንደተደረገ አድርጎ ይቆጥረዋል።—የሐዋርያት ሥራ 9:5
ዓመፀኛ እና አታላይ ሆኖ ሳለ በውሸት ክርስቲያን እንደሆነ ይናገራል።—ማቴዎስ 7:22, 23፤ 2 ቆሮንቶስ 11:13
መጽሐፍ ቅዱስ፣ እነዚህን ድርጊቶች የሚፈጽሙ ግለሰቦችን በተናጠል ፀረ ክርስቶሶች ብሎ ከመጥራት በተጨማሪ በጅምላ “ፀረ ክርስቶስ” ብሎ ይጠራቸዋል። (2 ዮሐንስ 7) ፀረ ክርስቶስ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገለጠው በሐዋርያት ዘመን ሲሆን ከዚያን ጊዜ አንስቶ በእንቅስቃሴ ላይ ይገኛል። መጽሐፍ ቅዱስ፣ ይህ እንደሚሆን አስቀድሞ ተናግሯል።—1 ዮሐንስ 4:3
ፀረ ክርስቶሶችን ለይቶ ማወቅ የሚቻልበት መንገድ
ስለ ኢየሱስ የሐሰት ትምህርቶችን ያስተምራሉ። (ማቴዎስ 24:9, 11) ለምሳሌ ያህል፣ ስለ ሥላሴ ወይም ኢየሱስ ሁሉን ቻይ አምላክ እንደሆነ የሚያስተምሩ ሁሉ የኢየሱስን ትምህርት ይቃወማሉ፤ ምክንያቱም ኢየሱስ “ከእኔ አብ ይበልጣል” ብሏል።—ዮሐንስ 14:28
ኢየሱስ ስለ አምላክ መንግሥት ያስተማረውን ነገር አይቀበሉም። ለምሳሌ አንዳንድ የሃይማኖት መሪዎች፣ ክርስቶስ በሰብዓዊ መንግሥታት አማካኝነት እንደሚገዛ ይናገራሉ። ሆኖም እንዲህ ያለው ትምህርት ኢየሱስ “መንግሥቴ የዚህ ዓለም ክፍል አይደለም” በማለት ከተናገረው ሐሳብ ጋር የሚጋጭ ነው።—ዮሐንስ 18:36
ኢየሱስ ጌታቸው እንደሆነ ይናገራሉ፤ ሆኖም ኢየሱስ የአምላክን መንግሥት ምሥራች እንድንሰብክ የሰጠውን ተልእኮ ጨምሮ ሌሎች የእሱን ትእዛዛት አያከብሩም።—ማቴዎስ 28:19, 20፤ ሉቃስ 6:46፤ የሐዋርያት ሥራ 10:42