በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የሽፋኑ ርዕሰ ጉዳይ | አምላክ ስለ አንተ ያስባል?

አምላክ ወደ አንተ መቅረብ ይፈልጋል

አምላክ ወደ አንተ መቅረብ ይፈልጋል

“የላከኝ አብ ካልሳበው በቀር ወደ እኔ ሊመጣ የሚችል ሰው የለም።”—ዮሐንስ 6:44

አንዳንዶች የሚጠራጠሩበት ምክንያት፦ በአምላክ የሚያምኑ ብዙ ሰዎች ወደ እሱ መቅረብ እንደማይችሉ ይሰማቸዋል። ክሪስቲና የምትባል በየሳምንቱ ቤተ ክርስቲያን የምትሄድ አንዲት አየርላንዳዊት እንዲህ ብላለች፦ “አምላክን የምመለከተው ሁሉንም ነገር እንደፈጠረ አካል አድርጌ ነው። ይሁን እንጂ ስለ እሱ የማውቀው ነገር አልነበረም። አንድም ቀን ወደ እሱ እንደቀረብኩ ተሰምቶኝ አያውቅም።”

የአምላክ ቃል ምን ያስተምራል? ግራ ገብቶን በምንባዝንበት ጊዜ ይሖዋ እኛን ለመርዳት ጥረት ማድረጉን አይተውም። ኢየሱስ አምላክ ለእኛ ያለውን አሳቢነት በሚከተለው ምሳሌ ገልጾታል፦ “አንድ ሰው መቶ በጎች ቢኖሩትና ከእነሱ አንዷ ብትጠፋ ዘጠና ዘጠኙን በተራራ ላይ ትቶ የጠፋችውን ለመፈለግ አይሄድም?” ትምህርቱ ምንድን ነው? “በተመሳሳይም በሰማይ ያለው አባቴ ከእነዚህ ከታናናሾቹ መካከል አንዱም እንዲጠፋ አይፈልግም።”—ማቴዎስ 18:12-14

‘እነዚህ ታናናሾቹ’ የተባሉት በሙሉ ለአምላክ እጅግ ውድ ናቸው። ታዲያ አምላክ “የጠፋችውን ለመፈለግ” የሚሄደው እንዴት ነው? በዚህ ርዕስ መግቢያ ላይ ያለው ጥቅስ እንደሚገልጸው ይሖዋ ሰዎችን ወደ ራሱ ይስባል።

በዛሬው ጊዜ ስለ አምላክ የሚገልጸውን የመጽሐፍ ቅዱስ መልእክት ሰዎች ቤት እየሄዱም ሆነ በአደባባይ የሚሰብኩት እነማን ናቸው?

አምላክ ቅን የሆኑ ሰዎችን ወደ ራሱ ለመሳብ ቀዳሚ ሆኖ እርምጃ የወሰደው እንዴት እንደሆነ ተመልከት። በአንደኛው መቶ ዘመን ዓ.ም. አምላክ፣ ፊልጶስ የተባለውን ክርስቲያን ወደ አንድ ኢትዮጵያዊ ባለሥልጣን ልኮት ነበር፤ ፊልጶስ የባለሥልጣኑ ሠረገላ ላይ ሮጦ ከደረሰ በኋላ ባለሥልጣኑ ሲያነበው ስለነበረው የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት ትርጉም አወያየው። (የሐዋርያት ሥራ 8:26-39) ከጊዜ በኋላም አምላክ፣ እየጸለየና እሱን ለማምለክ ጥረት እያደረገ ወደነበረ ቆርኔሌዎስ የሚባል አንድ ሮማዊ መኮንን ቤት እንዲሄድ ሐዋርያው ጴጥሮስን አዝዞታል። (የሐዋርያት ሥራ 10:1-48) በተጨማሪም አምላክ ሐዋርያው ጳውሎስንና ጓደኞቹን ከፊልጵስዩስ ከተማ ውጭ ወደሚገኝ አንድ ወንዝ እንዲሄዱ መርቷቸዋል። እዚያም ሊዲያ የምትባል “አምላክን የምታመልክ” ሴት ያገኙ ሲሆን “ይሖዋም ጳውሎስ የሚናገረውን በማስተዋል እንድትሰማ ልቧን በደንብ ከፈተላት።”—የሐዋርያት ሥራ 16:9-15

ከላይ ከተጠቀሱት ታሪኮች ማየት እንደሚቻለው ይሖዋ፣ እሱን ሲፈልጉ የነበሩት ሰዎች እሱን የማወቅ አጋጣሚ እንዲያገኙ አድርጓል። በዛሬው ጊዜስ ስለ አምላክ የሚገልጸውን የመጽሐፍ ቅዱስ መልእክት ሰዎች ቤት እየሄዱም ሆነ በአደባባይ የሚሰብኩት እነማን ናቸው? ብዙዎች “የይሖዋ ምሥክሮች ናቸው” ብለው መልስ ይሰጣሉ። አንተም ‘አምላክ ወደ እኔ ለመቅረብ እነዚህን ሰዎች እየተጠቀመባቸው ይሆን?’ ብለህ ራስህን ጠይቅ። አምላክ አንተን ወደ ራሱ ለመሳብ ለሚያደርገው ጥረት ቀና ምላሽ ለመስጠት እንዲረዳህ በጸሎት እንድትጠይቀው እንመክርሃለን። *

^ አን.8 ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት www.dan124.com/am በተባለው ድረ ገጻችን ላይ የሚገኘውን መጽሐፍ ቅዱስን መማር የሚኖርብን ለምንድን ነው? የተሰኘውን ቪዲዮ ተመልከት።