በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 47

ለመጠመቅ ዝግጁ ነህ?

ለመጠመቅ ዝግጁ ነህ?

መጽሐፍ ቅዱስን ስትማር ስለ ይሖዋ ብዙ ነገሮችን አውቀሃል። በተጨማሪም የተማርከውን ነገር ተግባር ላይ ለማዋል በሕይወትህ አንዳንድ ለውጦችን ሳታደርግ አትቀርም። ያም ሆኖ ራስህን ለይሖዋ ከመወሰንና ከመጠመቅ ወደኋላ እንድትል የሚያደርጉህ አንዳንድ ነገሮች ሊኖሩ ይችላሉ። በዚህ ምዕራፍ ላይ፣ ብዙዎች ከመጠመቅ ወደኋላ የሚሉባቸው አንዳንድ ምክንያቶች ምን እንደሆኑና እነዚህን እንቅፋቶች መወጣት የሚቻለው እንዴት እንደሆነ እንመለከታለን።

1. ከመጠመቅህ በፊት ምን ያህል እውቀት ሊኖርህ ይገባል?

ለመጠመቅ “የእውነትን ትክክለኛ እውቀት” ማግኘት ያስፈልግሃል። (1 ጢሞቴዎስ 2:4) እንዲህ ሲባል ግን ከመጠመቅህ በፊት፣ ሰዎች ለሚያነሷቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ጥያቄዎች በሙሉ ምን መልስ መስጠት እንዳለብህ ልታውቅ ይገባል ማለት አይደለም። ከተጠመቁ ብዙ ዓመት የሆናቸው ክርስቲያኖችም እንኳ መማራቸውን መቀጠል ይኖርባቸዋል። (ቆላስይስ 1:9, 10) ይሁንና መሠረታዊ የሆኑትን የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች ማወቅህ አስፈላጊ ነው። የጉባኤ ሽማግሌዎች በቂ እውቀት ይኖርህ እንደሆነና እንዳልሆነ ማወቅ እንድትችል ይረዱሃል።

2. ከመጠመቅህ በፊት ልትወስዳቸው የሚገቡ አንዳንድ እርምጃዎች የትኞቹ ናቸው?

ከመጠመቅህ በፊት ‘ንስሐ መግባትና መመለስ’ ይኖርብሃል። (የሐዋርያት ሥራ 3:19⁠ን አንብብ።) ይህም ሲባል ከዚህ በፊት ለፈጸምከው ኃጢአት ከልብ ልታዝንና ይሖዋ ይቅር እንዲልህ ልትለምን ይገባል ማለት ነው። በተጨማሪም አምላክ ከሚጠላቸው ነገሮች ለመራቅና እሱን በሚያስደስት መንገድ ለመኖር ቁርጥ ውሳኔ ማድረግ አለብህ። ከዚህም ሌላ በስብሰባዎች ላይ በመገኘትና ያልተጠመቅክ አስፋፊ ሆነህ በመስበክ በጉባኤው እንቅስቃሴዎች መሳተፍ ልትጀምር ይገባል።

3. ፍርሃት ወደኋላ እንዲያደርግህ ልትፈቅድ የማይገባው ለምንድን ነው?

አንዳንዶች ለይሖዋ ቃል የገቡትን ነገር ሳይፈጽሙ ሊቀሩ እንደሚችሉ ሲያስቡ ፍርሃት ያድርባቸዋል። እርግጥ ነው፣ አልፎ አልፎ ስህተት ልትሠራ እንደምትችል የታወቀ ነው፤ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሱ አንዳንድ ታማኝ ወንዶችና ሴቶችም ስህተት ሠርተዋል። ሆኖም ይሖዋ አገልጋዮቹ ፍጹም እንዲሆኑ አይጠብቅባቸውም። (መዝሙር 103:13, 14⁠ን አንብብ።) አቅምህ የፈቀደውን ሁሉ ስታደርግ ይደሰታል! ደግሞም ይረዳሃል። እንዲያውም ይሖዋ ምንም ነገር “[ከእሱ] ፍቅር ሊለየን እንደማይችል” አረጋግጦልናል።—ሮም 8:38, 39⁠ን አንብብ።

ጠለቅ ያለ ጥናት

ስለ ይሖዋ ይበልጥ ማወቅህና እሱ የሚሰጠውን እርዳታ መቀበልህ እንዳትጠመቅ እንቅፋት የሚሆንብህን ማንኛውንም ነገር ለማሸነፍ የሚረዳህ እንዴት እንደሆነ እንመለከታለን።

4. ስለ ይሖዋ ይበልጥ ለማወቅ ጥረት አድርግ

ከመጠመቅህ በፊት ስለ ይሖዋ ምን ያህል እውቀት ሊኖርህ ይገባል? ይሖዋን ለመውደድና እሱን በሚያስደስት መንገድ ለመኖር እንድትነሳሳ የሚያደርግ እውቀት ሊኖርህ ይገባል። በዓለም ዙሪያ ያሉ መጽሐፍ ቅዱስን የሚማሩ ሰዎች ለይሖዋ እንዲህ ያለ ፍቅር ማዳበር የቻሉት እንዴት እንደሆነ ለማየት ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • በቪዲዮው ላይ የታዩትን ሰዎች ለመጠመቅ ዝግጁ እንዲሆኑ የረዳቸው ምንድን ነው?

ሮም 12:2ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • መጽሐፍ ቅዱስ ወይም የይሖዋ ምሥክሮች ከሚያስተምሩት ነገር ጋር በተያያዘ እውነት ስለመሆኑ የምትጠራጠረው ነገር አለ?

  • ከሆነ ምን ማድረግ ትችላለህ?

5. እንዳትጠመቅ መሰናክል ሊሆኑብህ የሚችሉ ነገሮችን አሸንፍ

ሕይወታችንን ለይሖዋ ለመስጠትና ለመጠመቅ ስንወስን ሁላችንም መሰናክሎች ያጋጥሙናል። አንድ ምሳሌ ለማየት ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • በቪዲዮው ላይ ናራንጌረል ይሖዋን ለማገልገል የትኞቹን መሰናክሎች ማለፍ አስፈልጓታል?

  • ለይሖዋ ያላት ፍቅር መሰናክሎቹን እንድትወጣ የረዳት እንዴት ነው?

ምሳሌ 29:25ን እና 2 ጢሞቴዎስ 1:7ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • መሰናክሎችን ለመወጣት የሚያስፈልገንን ድፍረት ማግኘት የምንችለው እንዴት ነው?

6. ይሖዋ እንደሚረዳህ እምነት ይኑርህ

ይሖዋ እሱን ማስደሰት እንድትችል ይረዳሃል። ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • በቪዲዮው ላይ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪው ከመጠመቅ ወደኋላ ብሎ የነበረው ለምንድን ነው?

  • በይሖዋ ላይ ያለውን እምነት እንዲያጠናክር የረዳው ምን ማወቁ ነው?

ኢሳይያስ 41:10, 13ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ራስህን ስትወስን የገባኸውን ቃል መጠበቅ እንደምትችል እንድትተማመን የሚያደርግህ ምንድን ነው?

7. ይሖዋ ላሳየህ ፍቅር ያለህን አድናቆት አሳድግ

ይሖዋ ስላሳየህ ፍቅር ይበልጥ ባሰብክ መጠን ለእሱ ያለህ አድናቆትና እሱን ለዘላለም ለማገልገል ያለህ ፍላጎት እየጨመረ ይሄዳል። መዝሙር 40:5ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ይሖዋ ካደረገልህ ነገሮች መካከል አንተ ይበልጥ የምታደንቀው የትኞቹን ነው?

ነቢዩ ኤርምያስ ለይሖዋና ለቃሉ ጥልቅ ፍቅር ነበረው፤ በተጨማሪም የይሖዋን ስም መሸከም መቻሉን እንደ ትልቅ መብት ይመለከተው ነበር። እንዲህ ብሏል፦ “ይሖዋ ሆይ፣ በስምህ ተጠርቻለሁና፣ ቃልህ ሐሴት፣ ለልቤም ደስታ ሆነልኝ።” (ኤርምያስ 15:16) የሚከተሉትን ጥያቄዎች ለመመለስ ሞክር፦

  • የይሖዋ ምሥክር መሆን ትልቅ መብት የሆነው ለምንድን ነው?

  • ተጠምቀህ የይሖዋ ምሥክር መሆን ትፈልጋለህ?

  • ይህን እርምጃ እንዳትወስድ እንቅፋት የሚሆንብህ ነገር አለ?

  • ለመጠመቅ ብቁ ለመሆን ምን ማድረግ ያለብህ ይመስልሃል?

አንዳንዶች እንዲህ ይላሉ፦ “መጠመቅ የሚያስከትለውን ኃላፊነት መሸከም የምችል አይመስለኝም።”

  • አንተስ እንዲህ ይሰማሃል?

ማጠቃለያ

እንዳትጠመቅ እንቅፋት የሚሆንብህን ማንኛውንም ነገር በይሖዋ እርዳታ መወጣት ትችላለህ።

ክለሳ

  • ከመጠመቅህ በፊት ምን ያህል የመጽሐፍ ቅዱስ እውቀት ሊኖርህ ይገባል?

  • ከመጠመቅህ በፊት ምን ለውጦችን ማድረግ የሚኖርብህ ይመስልሃል?

  • ፍርሃት ወደኋላ እንዲያደርግህ መፍቀድ የሌለብህ ለምንድን ነው?

ግብ

ምርምር አድርግ

ለመጠመቅ ሊያነሳሳህ የሚገባው ምንድን ነው?

“ለመጠመቅ ዝግጁ ነህ?” (መጠበቂያ ግንብ መጋቢት 2020)

ከመጠመቅ ወደኋላ እንድትል የሚያደርጉህን ነገሮች ማሸነፍ የምትችለው እንዴት ነው?

“እንዳልጠመቅ የሚከለክለኝ ምን ነገር አለ?” (መጠበቂያ ግንብ መጋቢት 2019)

አንድ ሰው ከመጠመቅ ወደኋላ እንዲል አድርገውት የነበሩ ትላልቅ መሰናክሎችን በተሳካ ሁኔታ መወጣት የቻለው እንዴት ነው?

‘ከመጠመቅ ወደ ኋላ የምትለው ለምንድን ነው?’ (1:10)

አታ የተባለ አንድ ሰው መጀመሪያ ላይ ለመጠመቅ አመንትቶ ነበር። በኋላ ላይ ግን ይህን አስፈላጊ እርምጃ ለመውሰድ የተነሳሳው ለምንድን ነው?

በእርግጥ ይህ ይገባኛል? (7:21)