በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትክክል ወይም ስህተት ስለሆነው ነገር መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው መመሪያ በዘመናችንም ይሠራል?

ትክክል ወይም ስህተት ስለሆነው ነገር መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው መመሪያ በዘመናችንም ይሠራል?

 ክርስቲያን ነን የሚሉ አንዳንዶችን ጨምሮ ብዙ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ፆታ ግንኙነትና ስለ ጋብቻ የሚሰጣቸው የሥነ ምግባር መመሪያዎች ጊዜ እንዳለፈባቸው ይናገራሉ። አንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት በዘመናችን ተቀባይነት ያለውን አመለካከት ለማስተናገድ ሲሉ ትክክል ወይም ስህተት ስለሆነው ነገር የሚሰጡትን ትምህርት ቀይረዋል። ታዲያ ትክክል ወይም ስህተት ስለሆነው ነገር መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው መመሪያ በዘመናችንም ይሠራል? አዎ። ይህን የምንልበት ምክንያት ከዚህ ቀጥሎ ቀርቧል።

የሰው ልጆች ትክክል ወይም ስህተት ስለሆነው ነገር አምላክ የሚሰጠው መመሪያ ያስፈልጋቸዋል

 የሰው ልጆች የተፈጠሩት ከፈጣሪያቸው መመሪያ እንዲያገኙ ተደርገው ነው። መጽሐፍ ቅዱስ “[ሰው] አካሄዱን . . . በራሱ አቃንቶ መምራት አይችልም” ይላል። (ኤርምያስ 10:23) ይሖዋ a አምላክ፣ ውሳኔ የማድረግ ችሎታ እንዲኖረን አድርጎ ቢፈጥረንም ትክክል ወይም ስህተት የሆነውን ነገር የመወሰን ሥልጣንም ሆነ ችሎታ አልሰጠንም። በዚህ ረገድ መመሪያ ለማግኘት ወደ እሱ ዞር እንድንል ይፈልጋል።—ምሳሌ 3:5

 የአምላክን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች የምናገኘው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ነው። እነዚህ መሥፈርቶች በጣም ጠቃሚ የሆኑት ለምን እንደሆነ የሚያሳዩ ሁለት ምክንያቶችን እስቲ እንመልከት።

  •   የፈጠረን አምላክ ነው። (መዝሙር 100:3) ይሖዋ ፈጣሪያችን ነው፤ በመሆኑም ደስታ እንዲሁም አካላዊ፣ አእምሯዊና ስሜታዊ ጤንነት ማግኘት ከፈለግን ምን ማድረግ እንዳለብን ያውቃል። በተጨማሪም የእሱን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች ችላ ብንል ምን እንደሚያጋጥመን ያውቃል። (ገላትያ 6:7) ከዚህም ሌላ ይሖዋ በጣም ጥሩ ሕይወት እንድንመራ ይፈልጋል። አምላክ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ “የሚጠቅምህን ነገር የማስተምርህ፣ ልትሄድበትም በሚገባህ መንገድ የምመራህ እኔ . . . ነኝ” ያለው ለዚህ ነው።—ኢሳይያስ 48:17

  •   ልባችን ሊያሳስተን ይችላል። ብዙ ሰዎች፣ ልባቸው የሚላቸውን በመስማት ማለትም ስሜታቸውንና ምኞታቸውን በመከተል ትክክል ወይም ስህተት የሆነውን ነገር ለራሳቸው መወሰን እንደሚችሉ ያስባሉ። መጽሐፍ ቅዱስ ግን “ልብ ከምንም ነገር በላይ ከዳተኛ ነው፤ ማንኛውንም ነገር ከማድረግ አይመለስም” ይላል። (ኤርምያስ 17:9) ልባችንን በአምላክ ጥበብ ካልገራነው፣ የኋላ ኋላ ለጸጸት ወደሚዳርገን ጎዳና ሊመራን ይችላል።—ምሳሌ 28:26፤ መክብብ 10:2

የሃይማኖት መሪዎች ትክክል ወይም ስህተት ስለሆነው ነገር መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠውን መመሪያ ችላ ሊሉ ይገባል?

 በፍጹም! መጽሐፍ ቅዱስ ስለ አምላክ እውነቱን ያስተምረናል፤ በተጨማሪም አምላክ ከእኛ የሚጠብቀውን ምግባር ይገልጽልናል። (1 ቆሮንቶስ 6:9-11፤ ገላትያ 5:19-23) አምላክ፣ ሰዎች ይህን እውነት እንዲያውቁ ይፈልጋል። (1 ጢሞቴዎስ 2:3, 4) በመሆኑም ክርስቲያን አገልጋዮች ማስተማር ያለባቸው በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኘውን እውነት ነው።—ቲቶ 1:7-9

 የመጽሐፍ ቅዱስን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች መከተል የማይፈልጉ ብዙ ሰዎች፣ “መስማት የሚፈልጉትን [ወደሚነግሯቸው]” የሃይማኖት መሪዎች ዞር ይላሉ። (2 ጢሞቴዎስ 4:3 የግርጌ ማስታወሻ) ይሁንና የአምላክ ቃል “ጥሩውን መጥፎ፣ መጥፎውንም ጥሩ የሚሉ . . . ወዮላቸው!” የሚል ከባድ ማስጠንቀቂያ ይዟል። (ኢሳይያስ 5:20) በግልጽ ለማየት እንደሚቻለው አምላክ፣ ትክክል ወይም ስህተት የሆነውን ነገር በተመለከተ እሱ የሰጠውን መመሪያ በትክክል የማያስተምሩ የሃይማኖት መሪዎችን ይቀጣቸዋል።

የመጽሐፍ ቅዱስ የሥነ ምግባር መሥፈርቶች መቻቻልን ይከለክላሉ?

 በጭራሽ። አምላክን ማስደሰት የሚፈልጉ ሰዎች የኢየሱስ ክርስቶስን ምሳሌ እና ትምህርቶቹን ይከተላሉ። ኢየሱስ ተከታዮቹን በሌሎች ላይ እንዳይፈርዱ ከዚህ ይልቅ ለሁሉም ሰው ፍቅርና አክብሮት እንዲያሳዩ አስተምሯቸዋል።—ማቴዎስ 5:43, 44፤ 7:1

 የኢየሱስ ተከታዮች፣ ሕይወታቸውን በአምላክ የሥነ ምግባር መሥፈርቶች እንዲመሩ ይጠበቅባቸዋል። ያም ቢሆን ሌሎች ሰዎች ከእነሱ የተለየ መሥፈርት መከተል ሊፈልጉ እንደሚችሉ ኢየሱስ አስተምሯል። (ማቴዎስ 10:14) የኢየሱስ ተከታዮች በፖለቲካ ወይም በሌላ በማንኛውም መንገድ ተጠቅመው ሌሎች የአምላክን መሥፈርቶች እንዲቀበሉ የማስገደድ ሥልጣን አልተሰጣቸውም።—ዮሐንስ 17:14, 16፤ 18:36

የመጽሐፍ ቅዱስን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች መከተል ምን ጥቅም ያስገኛል?

 አምላክ ትክክል ወይም ስህተት ስለሆነው ነገር ያወጣቸውን መሥፈርቶች ለመከተል የሚጥሩ ሰዎች አሁንም ሆነ ለዘላለም በረከቶች ያገኛሉ። (መዝሙር 19:8, 11) ከእነዚህ በረከቶች አንዳንዶቹ የሚከተሉት ናቸው፦

a መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው የአምላክ የግል ስም ይሖዋ ነው።—መዝሙር 83:18