በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 14

አምላክ ድርጅት ያቋቋመው ለምንድን ነው?

አምላክ ድርጅት ያቋቋመው ለምንድን ነው?

1. አምላክ የጥንቶቹን እስራኤላውያን ያደራጃቸው ለምንድን ነው?

አምላክ የአብርሃምን ዘሮች በብሔር መልክ ካደራጃቸው በኋላ የሚመሩባቸውን ሕግጋት ሰጥቷቸዋል። ይህን ብሔር፣ “እስራኤል” ብሎ የጠራው ሲሆን እውነተኛውን አምልኮና ቅዱሳን መጻሕፍትን በአደራ ሰጥቷቸዋል። (መዝሙር 147:19, 20) በዚህ መንገድ ሁሉም ብሔራት ከእስራኤላውያን ጥቅም ማግኘት ችለዋል።​—ዘፍጥረት 22:18ን አንብብ።

አምላክ፣ እስራኤላውያንን ምሥክሮቹ እንዲሆኑ መርጧቸው ነበር። የእስራኤላውያን የጥንት ታሪክ፣ ሰዎች የአምላክን ሕግጋት ሲጠብቁ ጥቅም እንደሚያገኙ ያሳያል። (ዘዳግም 4:6) በመሆኑም የእነሱን ታሪክ በመመልከት ስለ እውነተኛው አምላክ ይበልጥ ማወቅ ይቻላል።​—ኢሳይያስ 43:10, 12ን አንብብ።

2. እውነተኛ ክርስቲያኖች መደራጀት ያስፈለጋቸው ለምንድን ነው?

ከጊዜ በኋላ እስራኤላውያን የአምላክን ሞገስ አጡ፤ በመሆኑም ይሖዋ ይህን ብሔር በመተው የክርስቲያን ጉባኤን አቋቋመ። (ማቴዎስ 21:43፤ 23:37, 38) በአሁኑ ጊዜ በጥንቶቹ እስራኤላውያን ምትክ እውነተኛ ክርስቲያኖች፣ የይሖዋ ምሥክሮች ሆነው ያገለግላሉ።​—የሐዋርያት ሥራ 15:14, 17ን አንብብ።

ኢየሱስ ምሥራቹን እንዲሰብኩና ከሁሉም ብሔራት ደቀ መዛሙርት እንዲያፈሩ ተከታዮቹን አደራጅቷቸው ነበር። (ማቴዎስ 10:7, 11፤ 24:14፤ 28:19, 20) አሁን ባለንበት በዚህ ሥርዓት መደምደሚያ ላይ ይህ ሥራ ወደ ፍጻሜው እየተቃረበ ነው። በታሪክ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ፣ ይሖዋ ከሁሉም ብሔራት የተውጣጡ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች በእውነተኛው አምልኮ አንድ እንዲሆኑ አድርጓል። (ራእይ 7:9, 10) እውነተኛ ክርስቲያኖች የተደራጁ መሆናቸው እርስ በርስ ለመበረታታትና ለመረዳዳት ያስችላቸዋል። በዓለም ዙሪያ በስብሰባዎቻቸው ላይ አንድ ዓይነት የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ይሰጣቸዋል።​—ዕብራውያን 10:24, 25ን አንብብ።

3. በዘመናችን ያለው የይሖዋ ምሥክሮች ድርጅት ሥራውን የጀመረው እንዴት ነው?

በ1870ዎቹ ዓመታት፣ የተወሰኑ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎችን ያቀፈ አንድ ትንሽ ቡድን ለብዙ ዓመታት ተዳፍነው የቆዩትን የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶች እንደገና ማግኘት ጀመረ። እነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች፣ ኢየሱስ የክርስቲያን ጉባኤን ያደራጀው በስብከቱ ሥራ እንዲካፈል እንደሆነ ስለተገነዘቡ በዓለም ዙሪያ ስለ አምላክ መንግሥት የመስበኩን ዘመቻ ተያያዙት። በ1931 እነዚህ ክርስቲያኖች፣ የይሖዋ ምሥክሮች በሚለው ስም መጠራት ጀመሩ።​—የሐዋርያት ሥራ 1:8ን፣ 2:1, 4ን እና 5:42ን አንብብ።

4. የይሖዋ ምሥክሮች የተደራጁት እንዴት ነው?

በአንደኛው መቶ ዘመን በበርካታ አገሮች ይገኙ የነበሩት የክርስቲያን ጉባኤዎች መመሪያ የሚያገኙት ከአንድ የበላይ አካል ሲሆን ይህ የበላይ አካል ኢየሱስን እንደ ጉባኤው ራስ አድርጎ ይመለከት ነበር። (የሐዋርያት ሥራ 16:4, 5) በተመሳሳይም በዛሬው ጊዜ በዓለም ዙሪያ ያሉ የይሖዋ ምሥክሮች፣ ተሞክሮ ያካበቱ ሽማግሌዎችን ያቀፈ የበላይ አካል ከሚሰጠው አመራር ጥቅም ያገኛሉ። ይህ የበላይ አካል መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት የሚረዱ ጽሑፎችን ከ600 በሚበልጡ ቋንቋዎች የሚተረጉሙ፣ የሚያትሙና የሚያሰራጩ ቅርንጫፍ ቢሮዎችን ሥራ ይከታተላል። በዚህ መንገድ የበላይ አካሉ ከ100,000 ለሚበልጡ በዓለም ዙሪያ የሚገኙ ጉባኤዎች ቅዱስ ጽሑፋዊ ማበረታቻና አመራር ይሰጣል። በእያንዳንዱ ጉባኤ ውስጥ ብቃት ያላቸው ወንዶች፣ ሽማግሌዎች ወይም የበላይ ተመልካቾች ሆነው ያገለግላሉ። እነዚህ ወንዶች የአምላክን መንጋ በፍቅር ይንከባከባሉ።​—1 ጴጥሮስ 5:2, 3ን አንብብ።

የይሖዋ ምሥክሮች የተደራጁት ምሥራቹን ለመስበክና ደቀ መዛሙርት ለማድረግ ነው። ልክ እንደ ሐዋርያት ከቤት ወደ ቤት እንሰብካለን። (የሐዋርያት ሥራ 20:20) በተጨማሪም እውነትን የሚወዱ ቅን ሰዎች ስናገኝ መጽሐፍ ቅዱስን እንዲያጠኑ እንጋብዛቸዋለን። የይሖዋ ምሥክሮች የአንድ ድርጅት አባላት ብቻ ከመሆን ባለፈ እንደ አንድ ቤተሰብ ነን። አፍቃሪ አባት ያለን ወንድማማችና እህትማማች በመሆናችን እርስ በርስ እንተሳሰባለን። (2 ተሰሎንቄ 1:3) የይሖዋ ሕዝቦች የተደራጁት አምላክን ለማስደሰትና ሌሎችን ለመርዳት በመሆኑ በምድር ላይ ከማንም በላይ ደስተኛ የሆነ ቤተሰብ አባላት መሆን ችለዋል።​—መዝሙር 33:12ን እና የሐዋርያት ሥራ 20:35ን አንብብ።